በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

በምዕራብ ኦሮሚያ የወባ ወረርሽኝ መባባሱ ተነገረ


የወባ ትንኝ
የወባ ትንኝ

አስከፊ ለሆነ የወባ ወረርሽኝ እና ለመድሃኒት እጥረት ተጋልጠናል ሲሉ በኦሮሚያ ክልል በቄለም ወለጋ እና በምዕራብ ወለጋ ዞኖች የሚገኙ ነዋሪዎች ለአሜሪካ ድምፅ ተናግረዋል።

ሰዎች በየቀኑ እንደሚሞቱ፣ በአካባቢው ያለው የፀጥታ ሁኔታ እና አካባቢውን በቀላሉ መድረስ አለመቻል ሁኔታውን እንዳባባሰው ነዋሪዎቹ ተናግረዋል።

ካለፈው ጥር ወዲህ በክልሉ 774 ሺሕ 519 ሰዎች በወባ የተያዙ መሆኑን እና 180 የሚሆኑ ሰዎች በበሽታው ምክንያት መሞታቸውን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብዓዊ ጉዳዮች ማስተባበሪያ ቢሮ (OCHA) አስታውቋል። ከ70 በመቶ በላይ የሚሆነው የተመዘገበው በምዕራብ ኦሮሚያ መሆኑን፣ በተለይም ምዕራብ ወለጋ እና ቄለም ወለጋ ተጠቃሽ መሆናቸውን ቢሮው ጨምሮ አስታውቋል።

ከመስከረም 7 እስከ 13 ባለው የአንድ ሳምንት ግዜ ውስጥ ብቻ፣ በክልሉ እስከ አሁን ከፍተኛ የተባለ የወባ ታማሚዎች ቁጥር መመዝገቡን የክልሉ ጤና ቢሮ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል። ለምርመራ ከቀረቡት 101 ሺሕ ከሚሆኑ ሰዎች ውስጥ 41ሺሕ 500 የሚሆኑት በወባ መያዛቸው ታውቋል።

ዝቅተኛ የገንዘብ ድጋፍ፣ የመድሓኒትና ሌሎች አቅርቦቶች እጥረት፣ እንዲሁም የጸጥታና አካባቢዎቹን በቀላሉ መድረስ አለመቻል ሁኔታውን እንዳባባሰው በዞኖቹ የሚገኙ የጤና ቢሮዎች አስታወቀዋል።

መድረክ / ፎረም

XS
SM
MD
LG