በቀላሉ የመሥሪያ ማገናኛዎች

መንፈቅ ሊሞላ የተቃረበው የእስራኤል ሀማስ ጦርነት ሌላ ዙር ድርድር በካይሮ ይደረጋል


በአውሮፓዊያኑ ሚያዚያ 2 ፣2024 የተነሳው ምስል ጋዛ ሰርጥ ውስጥ "ወርልድ ሴንትራል ኪችን " የተባለው የረድኤት ድርጅት ባልደረቦች የተገደሉበትን ስፍራ ነዋሪዎች ሲመለከቱ ያሳያል ።
በአውሮፓዊያኑ ሚያዚያ 2 ፣2024 የተነሳው ምስል ጋዛ ሰርጥ ውስጥ "ወርልድ ሴንትራል ኪችን " የተባለው የረድኤት ድርጅት ባልደረቦች የተገደሉበትን ስፍራ ነዋሪዎች ሲመለከቱ ያሳያል ።

የአሜሪካ እና እስራኤል ተደራዳሪዎች ፣ ወደ ግማሽ ዓመት በተጠጋው ጦርነት ውስጥ ተኩስ አቁም እና ታገቾችን በተመለከተ ስምምነት ላይ ይደረስ ዘንድ ሌላ ዙር ጫና ለማሳደር በሳምንቱ መገባደጃ ላይ ካይሮ ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል ።


ንግግሩ ከመጀመሩ አስቀድሞ የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚደንት ጆ ባይደን ለግብጽ እና ካታር መሪዎች ባደረሱት መልዕክት ፣ ሀማስ ስምምነቱን እንዲቀበል እና ተገዢ እንዲሆን ግፊት እንዲጨምሩ መጠየቃቸውን ፣ የባይደን አስተዳደር ከፍተኛ ባለስልጣን ለፈረንሳይ ዜና አገልግሎት ትናንት ምሽት አስታውቀዋል ።


የተኩስ አቁም ላይ እንዲደረስ እና ታጋቾችን በፍልስጤም እስረኞች ለማለዋወጥ የሚያስችል ስምምነት ላይ ይደረስ ዘንድ ዩናይትድ ስቴትስ፣ ካታር እና ግብጽ የጀርባ ንግግሮችን ሲያደርጉ ቆይተዋል ። ይሁንና በህዳር ወር ከነበረው ለሳምንት የዘለቀ ተግታ በቀር የስምምነቱ ጥረት ግስጋሴ አላሳየም ።

ዋይት ሀውስ የድርድር ሂደቱ በሳምንቱ መገባደጃ ካይሮ ውስጥ ሊቀጥል እንደሚችል ቢያረጋግጥም ፣ የአሜሪካ የዜና አውታሮች የዩናይትድ ስቴትስ መረጃ ማዕከል (ሲ አይ ኤ) ኃላፊ ቢል በርንስ ፣ የእስራኤል ስለላ ተቋም ኃላፊ ዴቪድ ባርኒያ ፣ የካታር ጠቅላይ ሚኒስትር ሞሐመድ ቢን አብዱራማን አል ታሃኒ እንዲሁም የግብጽ መረጃ ተቋም ኃላፊ አባስ ካመል በድርድሩ ላይ እንደሚገኙ በጠቅሰው በዘገቡት ዙሪያ ዋይት ሀውስ ማብራሪያ አልሰጠም ።

በሶስተኛ ወገን በኩል እየተደራደሩ ያሉት እስራኤል እና ሀማስ ፣ የድርድር ሂደቱ እርምጃ ላለማሳየቱ አንዳቸው አንዳቸውን ይወቅሳሉ ።

" ሀማስ ለጉዳት ተጋላጭ የሆኑ ታጋቾችን ማለትም ፣ የታመሙ ፣ የአካል ጉዳት የደረሰባቸውን ፣ አረጋዊያን እና ወጣት ሴቶችን ለመልቀቅ በቀላሉ ቢስማማ ኖሮ ፣ ዛሬ በጋዛ የተኩስ አቁም ይደረስ ነበር " ሲሉ ከፍተኛው ባለስልጣን አክለዋል ።

የሀማስ ባለስልጣናት እና የካታር አደራዳሪ አል ታሃኒ በበኩላቸው ቀደም ባለው ሳምንት ፣ እስራኤል ፣ የተፈናቀሉ የጋዛ ነዋሪዎች በሚመለሱበት ሁኔታ እና ፣ በታጋች - እስረኛ ልውውጥ ምጥጥን ዙሪያ ተቃውሞ በማንሳት ድርድሩን እንዳደናቀፈች በመግለጽ ከሰዋል ።

ባይደን ከእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኔጃሚን ኔታንያሁ ጋር በነበራቸው የስልክ ንግግር ፣ ኔታንያሁ ተደራዳሪዎቻቸው ስምምነት ላይ ይደርሱ ዘንድ ሁለንተናዊ ብቃት እንዲሰጧቸው ገፋፍተዋል ።

ጋዛ ውስጥ በቀጠለው ጦርነት ምክንያት እየጨመረ ያለው የጉዳት መጠን ፣ በተለይ ደግሞ የሰባት ረድዔት ሰራተኞችን መገደልን ተከትሎ የእስራኤል ጠንካራ ደጋፊ የሆኑት ባይደን ትዕግስት እየተማጠጠ ስለመምጣቱ ማሳያዎች ግልጽ ሆነዋል ።

የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ እና ሀገር ውስጡ ቁጣ ማየሉን ተከትሎ ፣ ባይደን ሰላማዊ ሰዎችን ለመጠበቅ ተጨማሪ እርምጃ የማይወሰድ ከሆነ ሀገራቸው ለእስራኤል የምትሰጠውን ድጋፍ ዳግም እንደምታጤን አስጠንቅቀዋል ።

(ዘገባው የፈረንሳይ አገልግሎት ነው )

መድረክ / ፎረም

XS
SM
MD
LG